ምዕራፍ 119
1በመንገዳቸው ንጹሐን የሆኑ፥ በእግዚአብሔርም ሕግ የሚሄዱ ምስጉኖች ናቸው።
2ምስክሩን የሚፈልጉ፥ በፍጹም ልብ የሚሹት ምስጉኖች ናቸው፤
3ዓመፅንም አያደርጉም፥ በመንገዶቹም ይሄዳሉ።
4ትእዛዛትህን እጅግ እንጠብቅ ዘንድ አንተ አዘዝህ።
5ሥርዓትህን ለመጠበቅ፤ መንገዶቼ ይቀኑ ዘንድ እወድድ ነበር።
6ትእዛዝህን ሁሉ ስመለከት በዚያን ጊዜ አላፍርም።
7አቤቱ፥ የጽድቅህን ፍርድ ስማር በቅን ልብ አመሰግንሃለሁ።
8ሥርዓትህን እጠብቃለሁ፤ በፍጹም አትጣለኝ። ቤት
9ጕልማሳ መንገዱን በምን ያነጻል? ቃልህን በመጠበቅ ነው።
10በፍጹም ልቤ ፈለግሁህ፥ ከትእዛዝህ አታርቀኝ።
11አንተ እንዳልበድል፥ ቃልህን በልቤ ሰወርሁ።
12አቤቱ፥ አንተ ቡሩክ ነህ፤ ሥርዓትህን አስተምረኝ።
13የአፍህን ፍርድ ሁሉ በከንፈሬ ነገርሁ።
14እንደ ብልጥግና ሁሉ በምስክርህ መንገድ ደስ አለኝ።
15ትእዛዝህን አሰላስላለሁ፥ መንገድህንም እፈልጋለሁ።
16በትእዛዝህ ደስ ይለኛል፤ ቃልህንም አልረሳም። ጋሜል
17ለባሪያህ መልካም አድርግ ሕያው እንድሆን፥ ቃልህንም እንድጠብቅ።
18ዓይኖቼን ክፈት፥ ከሕግህም ተኣምራትህን አያለሁ።
19እኔ በምድር እንግዳ ነኝ፤ ትእዛዛትህን ከእኔ አትሰውር።
20ነፍሴ ሁልጊዜ ፍርድህን እጅግ ናፈቀች።
21ከትእዛዛትህ የሳቱትን ትዕቢተኞችንና ርጉማንን ዘለፍህ።
22ምስክርህን ፈልጌአለሁና። ስድብንና ነውርን ከእኔ አርቅ።
23አለቆች ደግሞ ተቀምጠው እኔን አሙኝ፤ ባሪያህ ግን ሕግህን ያሰላስል ነበር።
24ምስክርህም ተድላዬ ነው፥ ሥርዓትህም መካሪዬ ነው። ዳሌጥ
25ነፍሴ ወደ ምድር ተጠጋች፤ እንደ ቃልህ ሕያው አድርገኝ።
26መንገድህን ነገርሁ ሰማኸኝም፤ ሥርዓትህን አስተምረኝ።
27የሥርዓትህን መንገድ እንዳስተውል አድርገኝ፥ ተኣምራትህንም አሰላስላለሁ።
28ከኀዘን የተነሣ ነፍሴ አንቀላፋች፤ በቃልህ አጠንክረኝ።
29የዓመፅን መንገድ ከእኔ አርቅ፥ በሕግህም ማረኝ፤
30የእውነትህን መንገድ መረጥሁ፥ ፍርድህንም አልረሳሁም።
31አቤቱ፥ ምስክርህን ተጠጋሁ፤ አታሳፍረኝ።
32ልቤን ባሰፋኸው ጊዜ፥ በትእዛዝህ መንገድ ሮጥሁ። ሄ
33አቤቱ፥ የሥርዓትህን መንገድ አስተምረኝ፥ ሁልጊዜም እፈልገዋለሁ።
34እንዳስተውል አድርገኝ፥ ሕግህንም እፈልጋለሁ፤ በፍጹም ልቤም እጠብቀዋለሁ።
35እርስዋን ወድጃለሁና የትእዛዝህን መንገድ ምራኝ።
36ልቤን ወደ ምስክርህ አዘንብል፥ ወደ ስስትም አይሁን።
37ከንቱ ነገርን እንዳያዩ ዓይኖቼን መልስ፤ በመንገድህ ሕያው አድርገኝ።
38እንዲፈራህ ባሪያህን በቃልህ አጽና።
39ፍርድህ መልካም ናትና የተጠራጠርሁትን ስድብ ከእኔ አርቅ።
40እነሆ፥ ትእዛዝህን ናፈቅሁ፤ በጽድቅህ ሕያው አድርገኝ ዋው
41አቤቱ፥ እንደ ቃልህ፥ ምሕረትህና መድኃኒትህ ይምጡልኝ።
42በቃልህ ታምኛለሁና ለሚሰድቡኝ በነገር እመልስላቸዋለሁ።
43በፍርድህም ታምኛለሁና የእውነትን ቃል ከአፌ ፈጽመህ አታርቅ።
44ለዘላለም ዓለም ሁልጊዜ ሕግህን እጠብቃለሁ።
45ትእዛዛትህንም ፈልጌአለሁና አስፍቼ እሄዳለሁ።
46በነገሥታት ፊት ምስክርህን እናገራለሁ፥ አላፍርምም፤
47እጅግም በወደድኋቸው በትእዛዛትህ ደስ ይለኛል።
48እጆቼንም ወደ ወደድኋቸው ወደ ትእዛዛትህ አነሣለሁ፤ ሥርዓትህንም አሰላስላሁ። ዛይ
49ለባሪያህ ተስፋ ያስደረግኸውን ቃልህን አስብ።
50ቃልህ ሕያው አድርጎኛልና ይህች በመከራዬ ደስ አሰኘችኝ።
51ትዕቢተኞች እጅግ ዐመፁ፤ እኔ ግን ከሕግህ አልራቅሁም።
52ከጥንት የነበረውን ፍርድህን አሰብሁ፥ አቤቱ፥ ተጽናናሁም።
53ሕግህን ከተዉ ከኃጢአተኞች የተነሣ ኅዘን ያዘኝ።
54በእንግድነቴ አገር ሥርዓትህ መዝሙር ሆነችኝ።
55አቤቱ፥ በሌሊት ስምህን አሰብሁ፥ ሕግህንም ጠበቅሁ።
56ትእዛዛትህንም ፈልጌአለሁና፤ ይህች ሆነችልኝ። ሔት
57እግዚአብሔር ክፍሌ ነው፤ ሕግህን እጠብቃለሁ አልሁ።
58በፍጹም ልቤ ወደ ፊትህ ተማለልሁ፤ እንደ ቃልህ ማረኝ።
59ስለ መንገዶችህ አሰብሁ፥ እግሬንም ወደ ምስክሮችህ መለስሁ።
60ትእዛዝህን ለመጠበቅ ጨከንሁ አልዘገየሁምም።
61የኃጥኣን ገመዶች ተተበተቡብኝ፤ ሕግህን ግን አልረሳሁም።
62ስለ ጽድቅህ ፍርድ፥ በእኩለ ሌሊት አመሰግንህ ዘንድ እነሣለሁ።
63እኔ ለሚፈሩህ ሁሉ፥ ትእዛዝህንም ለሚጠብቁ ባልንጀራ ነኝ።
64አቤቱ፥ ምሕረትህ በምድር ሁሉ ሞላች፤ ሥርዓትህን አስተምረኝ። ጤት
65አቤቱ፥ እንደ ቃልህ ለባሪያህ መልካም አደረግህ።
66በትእዛዛትህ ታምኛለሁና መልካም ምክርና እውቀትን አስተምረኝ።
67እኔ ሳልጨነቅ ሳትሁ፤ አሁን ግን ቃልህን ጠበቅሁ።
68አቤቱ፥ አንተ ቸር ነህ፥ በቸርነትህም ሥርዓትህን አስተምረኝ።
69የትዕቢተኞች ዓመፅ በላዬ በዛ፤ እኔ ግን በፍጹም ልቤ ትእዛዛትህን እፈልጋለሁ።
70ልባቸው እንደ ወተት ረጋ፤ እኔ ግን በሕግህ ደስ ይለኛል።
71ሥርዓትህን እማር ዘንድ ያስጨነቅኸኝ መልካም ሆነልኝ።
72ከአእላፋት ወርቅና ብር ይልቅ የአፍህ ሕግ ይሻለኛል። ዮድ
73እጆችህ ሠሩኝ አበጃጁኝም፤ እንዳስተውል አድርገኝ፥ ትእዛዛትህንም እማራለሁ።
74በቃልህ ታምኛለሁና የሚፈሩህ እኔን አይተው ደስ ይላቸዋል።
75አቤቱ፥ ፍርድህ ጽድቅ እንደ ሆነች፥ በእውነትህም እንዳስቸገርኸኝ አወቅሁ።
76ምሕረትህ ለመጽናናቴ ትሁነኝ፥ እንደ ቃልህም ለባሪያህ ይሁነው።
77ሕግህ ተድላዬ ናትና ቸርነትህ ትምጣልኝ፥ በሕይወትም ልኑር።
78ትዕቢተኞች በዓመፅ ጠምመውብኛልና ይፈሩ፤ እኔ ግን በትእዛዝህ እጫወታለሁ።
79የሚፈሩህና ምስክሮችህን የሚያውቁ ወደ እኔ ይመለሱ።
80እንዳላፍር ልቤ በሥርዓትህ የቀና ይሁን። ካፍ
81ነፍሴ መድኃኒትህን ናፈቀች፤ በቃልህም ታመንሁ።
82መቼ ታጽናናኛለህ እያልሁ ዓይኖቼ ስለ ቃልህ ፈዘዙ።
83በጢስ እንዳለ አቁማዳ ሆኛለሁና፤ ሥርዓትህን ግን አልረሳሁም።
84የባሪያህ ዘመኖች ስንት ናቸው? በሚያሳድዱኝስ ላይ መቼ ትፈርድልኛለህ?
85ኃጢአተኞች ጨዋታን ነገሩኝ፥ አቤቱ፥ እንደ ሕግህ ግን አይደለም።
86ትእዛዛትህ ሁሉ እውነት ናቸው፤ በዓመፅ አሳድደውኛል፤ እርዳኝ።
87ከምድር ሊያጠፉኝ ጥቂት ቀርቶአቸው ነበር፤ እኔ ግን ትእዛዛትህን አልተውሁም።
88እንደ ምሕረትህ ሕያው አድርገኝ፤ የአፍህንም ምስክር እጠብቃለሁ። ላሜድ
89አቤቱ፥ ቃልህ በሰማይ ለዘላለም ይኖራል።
90እውነትህ ለልጅ ልጅ ናት፤ ምድርን መሠረትሃት እርስዋም ትኖራለች።
91ሁሉም ባሪያዎችህ ናቸውና ቀኑ በትእዛዝህ ይኖራል።
92ሕግህ ተድላዬ ባይሆን፥ ቀድሞ በጐስቍልናዬ በጠፋሁ ነበር።
93በእርሱ ሕያው አድርገኸኛልና ፍርድህን ለዘላለም አልረሳም።
94እኔ የአንተ ነኝ፤ ፍርድህን ፈልጌአልሁና አድነኝ።
95ኃጢአተኞች ያጠፉኝ ዘንድ ጠበቁኝ፤ ምስክርህን ግን መረመርሁ።
96የሥራህን ሁሉ ፍጻሜ አየሁ፤ ትእዛዝህ ግን እጅግ ሰፊ ነው። ሜም
97አቤቱ፥ ሕግህን እንደ ምን እጅግ ወደድሁ! ቀኑን ሁሉ እርሱ ትዝታዬ ነው።
98ለዘላለም ለእኔ ነውና ትእዛዝህ ከጠላቶቼ ይልቅ አስተዋይ አደረገኝ።
99ምስክርህ ትዝታዬ ነውና ካስተማሩኝ ሁሉ ይልቅ አስተዋልሁ።
100ትእዛዝህን ፈልጌአለሁና ከሽማግሌዎች ይልቅ አስተዋልሁ።
101ቃልህን እጠብቅ ዘንድ ከክፉ መንገድ ሁሉ እግሬን ከለከልሁ።
102አስተምረኸኛልና ከፍርድህ አልራቅሁም።
103ቃልህ ለጕሮሮዬ ጣፋጭ ነው፤ ከማርና ከወለላ ይልቅ ለአፌ ጣፈጠኝ።
104ከትእዛዝህ የተነሣ አስተዋልሁ፤ ስለዚህ የሐሰትን መንገድ ጠላሁ። ኖን
105ሕግህ ለእግሬ መብራት፥ ለመንገዴ ብርሃን ነው።
106የጽድቅህን ፍርድ እጠብቅ ዘንድ ማልሁ፥ አጸናሁም።
107እጅግ ተቸገርሁ፤ አቤቱ፥ እንደ ቃልህ ሕያው አድርገኝ።
108አቤቱ፥ ከአፌ የሚወጣውን ቃል ውደድ፥ ፍርድህንም አስተምረኝ።
109ነፍሴ ሁልጊዜ በእጅህ ውስጥ ናት፤ ሕግህን ግን አልረሳሁም።
110ኃጢአተኞች ወጥመድን ዘረጉብኝ፤ ከትእዛዝህ ግን አልሳትሁም።
111የልቤ ደስታ ነውና ምስክርህን ለዘላለም ወረስሁ።
112ለዘላለም ለፍጻሜውም ትእዛዝህን አደርግ ዘንድ ልቤን አዘነበልሁ። ሳምኬት
113ዓመፀኞችን ጠላሁ፥ ሕግህን ግን ወደድሁ።
114አንተ ረዳቴና መጠጊያዬ ነህ፥ በቃልህም ተማመንሁ።
115እናንተ ኃጢአተኞች፥ ከእኔ ራቁ፥ የአምላኬንም ትእዛዝ ልፈልግ።
116እንደ ቃልህ ደግፈኝ፥ ሕያውም እሆናለሁ። ከተስፋዬም አልፈር።
117እርዳኝ እድናለሁም፥ ሁልጊዜም ሥርዓትህን እመረምራለሁ።
118ምኞታቸው ዓመፃ ነውና ከሥርዓትህ የሚርቁትን ሁሉ አጐሳቈልሃቸው።
119የምድርን ኃጢአተኞች ሁሉ እንደ ርኵሰት አጠፋሃቸው፤ ስለዚህ ምስክርህን ወደድሁ።
120ሥጋዬ አንተን ከመፍራት የተነሣ ደንገጠ፤ ከፍርድህ የተነሣ ፈርቻለሁ። ዔ
121ፍርድንና ጽድቅን ሠራሁ፤ ለሚያስጨንቁኝ አሳልፈህ አትስጠኝ።
122ባሪያህን በመልካም ጠብቀው፤ ትዕቢተኞችም አይጋፉኝ።
123ዓይኖቼ ለማዳንህ፥ ለጽድቅህም ቃል ፈዘዙ።
124ለባሪያህ እንደ ምሕረትህ አድርግ፥ ሥርዓትህንም አስተምረኝ።
125እኔ ባሪያህ ነኝ፤ እንዳስተውል አድርገኝ፥ ምስክርህንም አውቃለሁ።
126ለእግዚአብሔር የሥራ ጊዜ ነው፥ ሕግህንም ሻሩት።
127ስለዚህ ከወርቅና ከዕንቍ ይልቅ ትእዛዝህን ወደድሁ።
128ስለዚህ ወደ ትእዛዝህ ሁሉ አቀናሁ፥ የዓመፅንም መንገድ ሁሉ ጠላሁ። ፌ
129ምስክሮችህ ድንቆች ናቸው፤ ስለዚህ ነፍሴ ፈለገቻቸው።
130የቃልህ ፍቺ ያበራል፥ ሕፃናትንም አስተዋዮች ያደርጋል።
131አፌን ከፈትሁ፥ አለከለክሁም፤ ወደ ትእዛዝህ ናፍቄአለሁና።
132ስምህን ለሚወድዱ እንድምታደርገው ፍርድ፥ ወደ እኔ ተመልከተ ማረኝም።
133አካሄድን እንደ ቃልህ አቅና፤ ኃጢአትም ሁሉ አይግዛኝ።
134ከሰው ግፍ አድነኝ፤ ትእዛዝህንም እጠብቃለሁ።
135በባሪያህ ላይ ፊትህን አብራ፥ ሥርዓትህንም አሰተምረኝ።
136ሕግህን አልጠበቅሁምና የውኃ ፈሳሽ ከዓይኖቼ ፈሰሰ። ጻዴ
137አቤቱ፥ አንተ ጻድቅ ነህ፥ ፍርድህም ቅን ነው።
138ምስክርህን በጽድቅ አዘዝህ፥ እጅግም ቅን ነው።
139ጠላቶቼ ቃልህን ረስተዋልና የቤትህ ቅንዓት አቀለጠኝ።
140ቃልህ እጅግ የነጠረ ነው፥ ባሪያህም ወደደው።
141እኔ ታናሽና የተናቅሁ ነኝ፤ ትእዛዛትህን ግን አልረሳሁም።
142ጽድቅህ የዘላለም ጽድቅ ነው፥ ቃልህም እውነት ነው።
143መከራና ችግር አገኙኝ፤ ትእዛዛትህ ግን ተድላዬ ናቸው።
144ምስክርህ ለዘላለም ጽድቅ ነው፤ እንዳስተውል አድርገኝ፥ በሕይወትም አኑረኝ። ቆፍ
145በፍጹም ልቤ ጮኽሁ፥ አቤቱ፥ ስማኝ፤ ሥርዓትህን እፈልጋለሁ።
146ወደ አንተ ጮኽሁ፤ አድነኝ፥ ምስክርህንም እጠብቃለሁ።
147ማለዳ ጮኽሁ፤ ቃልህንም ተስፋ አድርጌአለሁ።
148ቃልህን አስብ ዘንድ ዓይኖቼ ለመማለድ ቀደሙ።
149አቤቱ፥ እንደ ቸርነትህ ድምፄን ስማ፤ እንደ ፍርድህ ሕያው አድርገኝ።
150በዓመፃ የሚያሳድዱኝ ቀረቡ፥ ከሕግህም ራቁ።
151አቤቱ፥ አንተ ቅርብ ነህ፥ መንገዶችህም ሁሉ ቅኖች ናቸው።
152ከዘላለም እንደ መሠረትኸው ከቀድሞ ጀምሮ ከምስክርህ የተነሣ አወቅሁ። ሬስ
153ሕግህን አልረሳሁምና ችግሬን ተመልከት አድነኝም።
154ፍርዴን ፍረድ አድነኝም፤ ስለ ቃልህ ሕያው አድርገኝ።
155መድኃኒት ከኅጥኣን ሩቅ ነው፥ ሥርዓትህን አልፈለጉምና።
156አቤቱ፥ ቸርነትህ እጅግ ብዙ ነው፤ እንደ ፍርድህ ሕያው አድርገኝ።
157ያሳደዱኝና ያስጨነቁኝ ብዙዎች ናቸው፤ ከምስክር ግን ፈቀቅ አላልሁም።
158ቃልህን አልጠበቁምና ሰነፎችን አይቼ አዘንሁ።
159ትእዛዝህን እንደ ወደድሁ ተመልከት፤ አቤቱ፥ በምሕረትህ ሕያው አድርገኝ።
160የቃልህ መጀመሪያ እውነት ነው፥ የጽድቅህንም ፍርድ ሁሉ ለዘላለም ነው። ሳን
161ገዢዎች በከንቱ አሳደዱኝ፤ ከቃልህ የተነሣ ግን ልቤ ደነገጠብኝ።
162ብዙ ምርኮ እንዳገኘ በቃልህ ደስ አለኝ።
163ዓመፃን ጠላሁ ተጸየፍሁም፤ ሕግን ግን ወደድሁ።
164ስለ ጽድቅህ ፍርድ ሰባት ጊዜ በቀን አመሰግንሃለሁ።
165ሕግህን ለሚወድዱ ብዙ ሰላም ነው፥ ዕንቅፋትም የለባቸውም።
166አቤቱ፥ ማዳንህን ተስፋ አደርግሁ፥ ትእዛዛትህንም ጠበቅሁ።
167ነፍሴ ምስክርህን ጠበቀች እጅግም ወደደችው።
168መንገዶቼ ሁሉ በፊትህ ናቸውና ትእዛዝህንና ምስክርህን ጠበቅሁ። ታው
169አቤቱ፥ ጸሎቴ ወደ ፊትህ ትቅረብ፤ እንደ ቃልህም አስተዋይ አድርገኝ።
170ልመናዬ ወደ ፊትህ ትድረስ፤ እንደ ቃልህ አድነኝ።
171ሥርዓትህን አስተምረኸኛልና ከንፈሮቼ ምስጋናን አወጡ።
172ትእዛዛትህ ሁሉ ጽድቅ ናቸውና አንደበቴ ቃልህን ተናገረ።
173ትእዛዛትህን መርጫለሁና እጅህ የሚያድነኝ ይሁን።
174አቤቱ፥ ማዳንህን ናፈቅሁ፤ ሕግህም ተድላዬ ነው።
175ነፍሴ ትኑርልኝ ታመሰግንህማለች፥ ፍርድህም ይርዳኝ።
176እንደ ጠፉ በግ ተቅበዘበዝሁ፤ ትእዛዛትህን አልረሳሁምና ባሪያህን ፈልገው።