English

ምዕራፍ 10

1[see v2]
2መበለቶችም ቅሚያቸው እንዲሆኑ፥ ድሀ አደጎችንም ብዝበዛቸው እንዲያደርጉ፥ የድሀውን ፍርድ ያጣምሙ ዘንድ፥ የችግረኛውንም ሕዝቤን ፍርድ ያጐድሉ ዘንድ የግፍን ትእዛዛት ለሚያዝዙ፥ ክፉንም ጽሕፈት ለሚጽፉ ወዮላቸው!
3በተጎበኛችሁበት ቀን፥ መከራም ከሩቅ በሚመጣበት ዘመን ምን ታደርጉ ይሆን? ለረድኤትስ ወደ ማን ትሸሻላችሁ? ክብራችሁንስ ወዴት ትተዉታላችሁ?
4ከእስረኞች በታች ይጐነበሳሉ፥ ከተገደሉትም በታች ይወድቃሉ። በዚህም ሁሉ እንኳ ቍጣው አልተመለሰችም፥ ነገር ግን እጁ ገና ተዘርግታ ትኖራለች።
5ለቍጣዬ በትር ለሆነ፥ የመዓቴም ጨንገር በእጁ ላለ ለአሦር ወዮለት!
6እርሱንም በዝንጉ ሕዝብ ላይ እልካለሁ፥ ምርኮውንና ብዝበዛውንም ይወስድ ዘንድ እንደ አደባባይም ጭቃ የተረገጡ ያደርጋቸው ዘንድ በምቈጣቸው ሰዎች ላይ አዝዘዋለሁ።
7እርሱ እንዲሁ አያስብም፥ በልቡም እንዲህ አይመስለውም፤ ነገር ግን ማጥፋት፥ ጥቂት ያይደሉትንም አሕዛብን መቍረጥ በልቡ አለ።
8እንዲህ ይላል። መሳፍንቴ ሁሉ ነገሥታት አይደሉምን? ካልኖ እንደ ከርከሚሽ አይደለችምን?
9ሐማትስ እንደ አርፋድ አይደለችምን? ሰማርያስ እንደ ደማስቆ አይደለችምን?
10የተቀረጹ ምስሎቻቸው ከኢየሩሳሌምና ከሰማርያ ምስሎች የበለጡትን የጣዖቶችን መንግሥታት እጄ እንዳገኘች፥
11በሰማርያና በጣዖቶችዋም እንዳደረግሁ፥ እንዲሁስ በኢየሩሳሌምና በጣዖቶችዋ አላደርግምን?
12ስለዚህ እንዲህ ይሆናል፤ ጌታ ሥራውን ሁሉ በጽዮን ተራራና በኢየሩሳሌም ላይ በፈጸመ ጊዜ የአሦርን ንጉሥ የኩሩ ልብ ፍሬን የዓይኑንም ከፍታ ትምክሕት ይጐበኛል።
13እርሱ እንዲህ ብሎአልና። አስተዋይ ነኝና በእጄ ኃይልና በጥበቤ አደረግሁት፤ የአሕዛብን ድንበሮች አራቅሁ፥ ሀብታቸውንም ዘረፍሁ፥ እንደ ጀግናም ሆኜ በምድር የተቀመጡትን አዋረድሁ፤
14እጄም የአሕዛብን ኃይል እንደ ወፍ ቤት አገኘች፤ የተተወም እንቍላል እንደሚሰበሰብ እንዲሁ እኔ ምድርን ሁሉ ሰበሰብሁ፤ ክንፉን የሚያራግብ አፉንም የሚከፍት የሚጮኽም የለም።
15በውኑ መጥረቢያ በሚቈርጥበት ሰው ላይ ይመካልን? ወይስ መጋዝ በሚስበው ላይ ይጓደዳልን? ይህስ፥ በትር የሚያነሣውን እንደ መነቅነቅ ዘንግም እንጨት ያይደለውን እንደ ማንሣት ያህል ነው።
16ስለዚህም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በወፍራሞች ላይ ክሳትን ይልካል፤ ከክብሩም በታች ቃጠሎው እንደ እሳት መቃጠል ይነድዳል።
17የእስራኤልም ብርሃን እንደ እሳት ቅዱስም እንደ ነበልባል ይሆናል፤ እሾሁንና ኵርንችቱን በአንድ ቀን ያቃጥላል ይበላውማል።
18ከነፍስም እስከ ሥጋ ድረስ የዱሩንና የሚያፈራውን እርሻ ክብር ይበላል፤ ይህም የታመመ ሰው እንደሚሰለስል ይሆናል።
19የቀሩትም የዱር ዛፎች በቍጥር ጥቂት ይሆናሉ፥ ታናሽ ብላቴናም ይጽፋቸው ዘንድ ይችላል።
20በዚያም ቀን እንዲህ ይሆናል፤ የእስራኤል ቅሬታ ከያዕቆብም ቤት የዳኑት ከእንግዲህ ወዲህ በመቱአቸው ላይ አይደገፉም፤ ነገር ግን በእስራኤል ቅዱስ በእግዚአብሔር ላይ በእውነት ይደገፋሉ።
21የያዕቆብም ቅሬታ ወደ ኃያል አምላክ ይምለሳሉ።
22እስራኤል ሆይ፥ የሕዝብህ ቍጥር እንደ ባሕር አሸዋ ቢሆን ቅሬታው ይመለሳል። ጽድቅ የተትረፈረፈበትም ጥፋት ተወስኖአል።
23የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔርም ያለቀ የተቈረጠ ነገርን በምድር ሁሉ መካከል ይፈጽማል።
24ስለዚህ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በጽዮን የምትኖር ሕዝቤ ሆይ፥ አሦር በበትር ቢመታህ፥ ግብጽም እንዳደረገ ዘንጉን ቢያነሣብህ አትፍራው።
25ቍጣዬ እስኪፈጸም መዓቴም እስኪያጠፋቸው ድረስ ጥቂት ጊዜ ቀርቶአልና።
26የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔርም ምድያምን በሔሬብ ዓለት በኩል እንደ መታው ጅራፍ ያነሣበታል፤ በትሩም በባሕር ላይ ይሆናል፥ በግብጽም እንዳደረገ ያነሣዋል።
27በዚያም ቀን ሸክሙ ከጫንቃህ ቀንበሩም ከአንገትህ ላይ ይወርዳል፤ ቀንበሩም ከውፍረት የተነሣ ይሰበራል።
28ወደ አንጋይ መጥቶአል፤ በመጌዶን በኩል አልፎአል፤ በማክማስ ውስጥ ዕቃውን አኑሮአል፤
29በመተላለፊያ አልፎአል፤ በጌባ ማደሪያው ነው፤ ራማ ደንግጣለች፤ የሳኦል ጊብዓ ኰብልላለች።
30አንቺ የጋሊም ልጅ ሆይ፥ በታላቅ ድምፅሽ ጩኺ፤ ላይሳ ሆይ፥ አድምጪ፤ ዓናቶት ሆይ፥ መልሽላት።
31መደቤና ሸሽታለች፤ በግቤርም የሚኖሩ ቤተ ሰቦቻቸውን አሽሽተዋል።
32ዛሬ በኖብ ይቆማል፤ በጽዮን ሴት ልጅ ተራራ በኢየሩሳሌም ኮረብታ ላይ እጁን ያንቀሳቅሳል።
33እነሆ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ቅርንጫፎቹን በሚያስፈራ ኃይል ይቈርጣል፤ በቁመት የረዘሙትም ይቈረጣሉ፥ ከፍ ያሉትም ይዋረዳሉ።
34ጭፍቅ የሆነውንም ዱር በብረት ይቈርጣል፥ ሊባኖስም በኃያሉ እጅ ይወድቃል።