ምዕራፍ 4
1ሙሴም መለሰ። እነሆ አያምኑኝም ቃሌንም አይሰሙም። እግዚአብሔር ከቶ አልተገለጠልህም ይሉኛል አለ።
2እግዚአብሔርም። ይህች በእጅህ ያለችው ምንድር ናት? አለው። እርሱም። በትር ናት አለ።
3ወደ መሬት ጣላት አለው፤ እርሱም በመሬት ጣላት፥ እባብም ሆነች፤ ሙሴም ከእርሷ ሸሸ።
4
5እግዚአብሔርም ሙሴን። የአባቶቻቸው አምላክ፥ የአብርሃም አምላክ የይስሐቅም አምላክ የያዕቆብም አምላክ፥ እግዚአብሔር እንደ ተገለጠልህ እንዲያምኑ እጅህን ዘርግተህ ጅራትዋን ያዝ አለው። እጁንም ዘርግቶ ያዛት በእጁም ውስጥ በትር ሆነች።
6እግዚአብሔርም ደግሞ። እጅህን ወደ ብብትህ አግባ አለው። እጁንም ወደ ብብቱ አገባት፤ ባወጣትም ጊዜ እነሆ፥ እጁ እንደ በረዶ ለምጽ ሆነች።
7እርሱም። እጅህን ወደ ብብትህ መልስ አለው። እጁንም ወደ ብብቱ መለሳት፥ ከብብቱም ባወጣት ጊዜ እነሆ ተመልሳ ገላውን መሰለች።
8ደግሞም አለው። እንዲህም ይሆናል፤ ባያምኑህ የፊተኛይቱንም ምልክት ነገር ባይሰሙ፥ የሁለተኛይቱን ምልክት ነገር ያምናሉ።
9እንዲህም ይሆናል፤ እነዚህን ሁለት ምልክቶች ባያምኑ ቃልህንም ባይሰሙ፥ ከወንዙ ውኃን ውሰድ፥ በደረቁም መሬት ላይ አፍስሰው፤ ከወንዙም የወሰድኸው ውኃ በደረቁ መሬት ላይ ደም ይሆናል።
10ሙሴም እግዚአብሔርን። ጌታ ሆይ፥ እኔ አፌ ኰልታፋ ምላሴም ጸያፍ የሆነ ሰው ነኝ፤ ትናንት ከትናንት ወዲያ ባሪያህንም ከተናገርኸኝ ጀምሮ አፈ ትብ ሰው አይደለሁም።
11እግዚአብሔርም። የሰውን አፍ የፈጠረ ማን ነው? ዲዳስ ደንቆሮስ የሚያይስ ዕውርስ ያደረገ ማን ነው? እኔ እግዚአብሔር አይደለሁምን?
12እንግዲህ አሁን ሂድ፥ እኔም ከአፍህ ጋር እሆናለሁ፥ የምትናገረውንም አስተምርሃለሁ አለው።
13እርሱም። ጌታ ሆይ፥ በምትልከው ሰው እጅ ትልክ ዘንድ እለምንሃለሁ አለ።
14የእግዚአብሔርም ቍጣ በሙሴ ላይ ነደደ እንዲህም አለ። ሌዋዊው ወንድምህ አሮን አለ አይደለምን? እርሱ ደህና እንዲናገር አውቃለሁ፤ እነሆም ደግሞ ሊገናኝህ ይመጣል፤ ባየህም ጊዜ በልቡ ደስ ይለዋል።
15አንተም ትናገረዋለህ ቃሉንም በአፉ ታደርገዋለህ፤ እኔ ከአፍህና ከአፉ ጋር እሆናለሁ፥ የምታደርጉትንም አስተምራችኋለሁ።
16እርሱ ስለ አንተ ከሕዝቡ ጋር ይናገራል፤ እንዲህም ይሆናል፤ እርሱ አፍ ይሆንልሃል አንተም በእግዚአብሔር ፋንታ ትሆንለታለህ።
17ይህችንም ተአምራት የምታደርግባትን በትር በእጅህ ይዘሃት ሂድ።
18ሙሴም ሄደ፥ ወደ አማቱ ወደ ዮቶር ተመለሰ። እስከ ዛሬ በሕይወት እንዳሉ አይ ዘንድ ተመልሼ ወደ ግብፅ ወደ ወንድሞቼ ልሂድ አለው። ዮቶርም ሙሴን። በሰላም ሂድ አለው።
19እግዚአብሔርም ሙሴን በምድያም። ነፍስህን የሚሹአት ሰዎች ሁሉ ሞተዋልና ተመልሰህ ወደ ግብፅ ሂድ አለው።
20ሙሴም ሚስቱንና ልጆቹን ወሰደ፥ በአህያ ላይም አስቀመጣቸው፥ ወደ ግብፅም አገር ተመለሰ፤ ሙሴም የእግዚአብሔርን በትር ይዞ ሄደ።
21እግዚአብሔርም ሙሴን አለው። ወደ ግብፅ ስትመለስ በእጅህ ያደረግሁትን ተአምራት ሁሉ በፈርዖን ፊት ታደርገው ዘንድ ተመልከት፤ እኔ ግን ልቡን አጸናዋለሁ፥ ሕዝቡንም አይለቅቅም።
22ፈርዖንንም። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል።
23እስራኤል የበኵር ልጄ ነው፤ ይገዛልኝ ዘንድ ልጄን ልቀቅ አልሁህ፤ አንተም ትለቅቀው ዘንድ እንቢ አልህ፤ እነሆ እኔ የበኵር ልጅህን እገድላለሁ ትለዋለህ።
24እንዲህም ሆነ፤ በመንገድ ላይ ባደረበት ስፍራ እግዚአብሔር ተገናኘው፥ ሊገድለውም ፈለገ።
25ሲፓራም ሚስቱ ባልጩት ወሰደች፥ የልጅዋንም ሸለፈት ገረዘች፥ ወደ እግሩም ጣለችው። አንተ ለእኔ የደም ሙሽራ ነህ አለች።
26ከእርሱም ፈቀቅ አለ። የዚያን ጊዜ። ስለ ግርዛቱ አንተ የደም ሙሽራ ነህ አለች።
27እግዚአብሔርም አሮንን። ሄደህ በምድረ በዳ ሙሴን ተገናኘው አለው፤ ሄዶም በእግዚአብሔር ተራራ ተገናኘው፥ ሳመውም።
28ሙሴም እግዚአብሔር በእርሱ ዘንድ የላከውን ቃል ሁሉ ያዘዘውንም ተአምራት ሁሉ ለአሮን ተናገረው።
29ሙሴና አሮንም ሄዱ የእስራኤልንም ልጆች ሽማግሌዎች ሁሉ ሰበሰቡ።
30አሮንም እግዚአብሔር ለሙሴ የነገረውን ቃል ሁሉ ተናገረ፥ ተአምራቱንም በሕዝቡ ፊት አደረገ።
31ሕዝቡም አመኑ፤ እግዚአብሔርም የእስራኤልን ልጆች እንደ ጐበኘ ጭንቀታቸውንም እንዳየ በሰሙ ጊዜ፥ አጐነበሱ ሰገዱም።