ምዕራፍ 121
1ዓይኖቼ ወደ ተራሮች አነሣሁ፤ ረዳቴ ከወዴት ይምጣ?
2ረዳቴ ሰማይና ምድርን ከሠራ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው።
3እግርህን ለመናወጥ አይሰጠውም፤ የሚጠብቅህም አይተኛም።
4እነሆ፥ እስራኤልን የሚጠብቅ አይተኛም አያንቀላፋምም።
5እግዚአብሔር ይጠብቅሃል፥ እግዚአብሔርም በቀኝ እጅህ በኩል ይጋርድሃል።
6ፀሐይ በቀን አያቃጥልህም ጨረቃም በሌሊት።
7እግዚአብሔር ከክፉ ሁሉ ይጠብቅሃል፥ ነፍስህንም ይጠብቃታል።
8ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም እግዚአብሔር መውጣትህና መግባትህን ይጠብቃል።