English

ምዕራፍ 22

1መልካም ስም ከብዙ ባለጠግነት ይሻላል፥ መልካምም ሞገስ ከብርና ከወርቅ ይበልጣል።
2ባለጠና ድሀ ተገናኙ፤ እግዚአብሔር የሁላቸው ፈጣሪ ነው።
3ብልህ ሰው ክፉን አይቶ ይሸሸጋል፤ አላዋቂዎች ግን አልፈው ይጐዳሉ።
4ትሕትናና እግዚአብሔርን መፍራት ባለጠግነት ክብር ሕይወትም ነው።
5እሾህና ወጥመድ በጠማማ ሰው መንገድ ናቸው፤ ነፍሱን ግን የሚጠብቅ ከእነርሱ ይርቃል።
6ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው፥ በሸመገለም ጊዜ ከእርሱ ፈቀቅ አይልም።
7ባለጠጋ ድሆችን ይገዛል፥ ተበዳሪም የአበዳሪ ባሪያ ነው።
8ኃጢአትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል፥ የቍጣውም በትር ይጠፋል።
9ርኅሩህ የተባረከ ይሆናል፥ ከእንጀራው ለድሀ ሰጥቶአልና።
10ፌዘኛን ብታወጣ ክርክር ይወጣል፥ ጠብና ስድብም ያልቃል።
11የልብን ንጽሕና የሚወድድና ሞገስ በከንፈሩ ያለች፥ ንጉሥ ወዳጁ ይሆናል።
12የእግዚአብሔር ዓይኖች እውቀትን ይጠብቃሉ፤ እርሱ ግን የወስላታውን ቃል ይገለብጣል።
13ታካች ሰው። አንበሳ በሜዳ ነው፤ በመንገዱ ላይ እሞታለሁ ይላል።
14የጋለሞታ ሴት አፍ የጠለቀ ጕድጓድ ነው፤ እግዚአብሔር የተቈጣው በእርስዋ ይወድቃል።
15ስንፍና በሕፃን ልብ ታስሮአል፤ የተግሣጽ በትር ግን ከእርሱ ያርቃታል።
16ለራሱ ጥቅም ለመጨመር ሲል ድሀን የሚጐዳ፥ ለባለጠጋም የሚሰጥ፥ እርሱ ወደ ድህነት ይወድቃል።
17ጆሮህን አዘንብለህ የጠቢባንን ቃላት ስማ፥ ልብህንም ወደ እውቀቴ አድርግ፤
18እነርሱን በውስጥህ ብትጠብቅ፥ በከንፈሮችህም ላይ የተዘጋጁ ቢሆኑ፥ የተወደደ ነገር ይሆንልሃልና።
19እምነትህ በእግዚአብሔር ይሆን ዘንድ ለአንተ ዛሬ እነሆ አስታወቅሁህ።
20-
21የእውነትን ቃል እርግጥነት አስታውቅህ ዘንድ፥ ለሚጠይቅህም እውነትን ቃል መመለስ ይቻልህ ዘንድ፥ በምክርና በእውቀት የከበረን ነገር አልጻፍሁልህምን?
22ድሀን በግድ አትበለው ድሀ ነውና፤ ችግረኛውንም በበር አትግፋው፤
23እግዚአብሔር የእነርሱን ፍርድ ይፋረድላቸዋልና፥ የቀሙአቸውንም ሰዎች ሕይወት ይቀማልና።
24ከቍጡ ሰው ጋር ባልንጀራ አትሁን፥ ከወፈፍተኛም ጋት አትሂድ፥
25መንገዱን እንዳትማር ለነፍስህም ወጥመድ እንዳታገኝህ።
26እጃቸውን አጋና እንደሚማቱ፥ ለባለ ዕዳዎች እንደሚዋሱ አትሁን፤
27የምትከፍለው ባይኖርህ፥ ምንጣፍህን ከበታችህ ስለ ምን ይወስዳል?
28አባቶችህ የሠሩትን የቀድሞውን የድንበር ምልክት አታፍልስ።
29በሥራው የቀጠፈ ሰውን አይተሃልን? በነገሥታት ፊት ይቆማል፤ በተዋረዱም ሰዎች ፊት አይቆምም።